ረቡዕ፣ ግንቦት 24
በሙሉ ልብህ በይሖዋ ታመን፤ ደግሞም በገዛ ራስህ ማስተዋል አትመካ።—ምሳሌ 3:5
ባሎች ቤተሰባችሁን የመንከባከብ ኃላፊነት ስላለባችሁ ቤተሰባችሁን ከጉዳት ለመጠበቅና ለማስተዳደር ተግታችሁ ትሠራላችሁ። ተፈታታኝ ሁኔታዎች ሲያጋጥሟችሁ ችግሩን በራሳችሁ መፍታት እንደምትችሉ ይሰማችሁ ይሆናል። ሆኖም በራሳችሁ ብርታት አትመኩ። ከዚህ ይልቅ ይሖዋ እንዲረዳችሁ በግላችሁ ጸልዩ። በተጨማሪም ከሚስታችሁ ጋር ሆናችሁ አጥብቃችሁ ጸልዩ። መጽሐፍ ቅዱስን እና ድርጅቱ ያዘጋጃቸውን ጽሑፎች በማጥናት ከይሖዋ መመሪያ ለማግኘት ጥረት አድርጉ፤ እንዲሁም ያገኛችሁትን ምክር በሥራ ላይ አውሉ። እርግጥ ባደረጋችሁት በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ የተመሠረተ ውሳኔ ሌሎች አይስማሙ ይሆናል። የቤተሰባችሁን ደህንነት ማስጠበቅ የምትችሉት ገንዘብና ቁሳዊ ነገር ሲኖራችሁ እንደሆነ ይነግሯችሁ ይሆናል። ሆኖም የንጉሥ ኢዮሳፍጥን ምሳሌ አስታውሱ። (2 ዜና 20:1-30) ኢዮሳፍጥ በይሖዋ ታምኗል፤ እምነቱንም በተግባር አሳይቷል። ይሖዋ ያንን ታማኝ ሰው አልተወውም፤ እናንተንም ቢሆን አይተዋችሁም።—መዝ. 37:28፤ ዕብ. 13:5፤ w21.11 15 አን. 6፤ 16 አን. 8
ሐሙስ፣ ግንቦት 25
[አምላክ] ፈጽሞ ፍትሕን [አያጓድልም።]—ዘዳ. 32:4
አምላክ በመልኩ ስለፈጠረን ሁሉም ሰው ፍትሕ ሲያገኝ ማየት እንፈልጋለን። (ዘፍ. 1:26) ሆኖም ፍጹም ባለመሆናችን፣ ስለ አንድ ጉዳይ በደንብ እንደምናውቅ በሚሰማን ጊዜም እንኳ የተሳሳተ መደምደሚያ ላይ ልንደርስ እንችላለን። ለምሳሌ ያህል፣ ዮናስ ይሖዋ ለነነዌ ሰዎች ምሕረት ለማሳየት በመወሰኑ ምን ያህል እንደተበሳጨ አስታውሱ። (ዮናስ 3:10 እስከ 4:1) ውጤቱን ግን አስቡት። ንስሐ የገቡ ከ120,000 የሚበልጡ የነነዌ ሰዎች ሕይወታቸው ተረፈ! መጨረሻውንም አመለካከቱን ማስተካከል ያስፈለገው ዮናስ እንጂ ይሖዋ አይደለም። ይሖዋ ውሳኔ ያደረገበትን ምክንያት ለሰዎች የማብራራት ግዴታ የለበትም። እርግጥ ነው፣ ይሖዋ በጥንት ዘመን የነበሩ አገልጋዮቹ ስላደረጋቸው ወይም ሊያደርጋቸው ስላሰባቸው ውሳኔዎች ያሳሰባቸውን ነገር እንዲገልጹ ፈቅዶላቸዋል። (ዘፍ. 18:25፤ ዮናስ 4:2, 3) ውሳኔውን ያደረገበትን ምክንያት ያብራራበት ጊዜም አለ። (ዮናስ 4:10, 11) ያም ቢሆን ይሖዋ ውሳኔ ከማድረጉ በፊትም ሆነ በኋላ የእኛን ይሁንታ ማግኘት አያስፈልገውም።—ኢሳ. 40:13, 14፤ 55:9፤ w22.02 3-4 አን. 5-6
ዓርብ፣ ግንቦት 26
ከእናንተ መካከል ታላቅ የሆነ እንደ ታናሽ ይሁን፤ አመራር የሚሰጥም እንደ አገልጋይ ይሁን።—ሉቃስ 22:26
‘ሌሎች ከእኛ እንደሚበልጡ’ አድርገን የምናስብ ከሆነ ራሳችንን “እንደ ታናሽ” እንደምንቆጥር በተግባር እናሳያለን። (ፊልጵ. 2:3) ይህን አመለካከት ይበልጥ ባዳበርን መጠን ሌሎችን ላለማሰናከል ይበልጥ ጥንቃቄ እናደርጋለን። ሁሉም ወንድሞቻችን እና እህቶቻችን በሆነ መንገድ ከእኛ ይበልጣሉ። ባሏቸው መልካም ባሕርያት ላይ የምናተኩር ከሆነ ይህን ማስተዋል አይከብደንም። ሐዋርያው ጳውሎስ ለቆሮንቶስ ክርስቲያኖች የሰጣቸውን የሚከተለውን ምክር ልብ ልንለው ይገባል፦ “ለመሆኑ አንተን ከሌላው የተለየህ እንድትሆን ያደረገህ ማን ነው? ደግሞስ ያልተቀበልከው ምን ነገር አለ? ከተቀበልክ ደግሞ እንዳልተቀበልክ ሆነህ የምትኩራራው ለምንድን ነው?” (1 ቆሮ. 4:7) ወደ ራሳችን ትኩረት የመሳብ ወይም ከሌሎች እንደምንበልጥ አድርገን የማሰብ ዝንባሌ እንዳይኖረን መጠንቀቅ ይኖርብናል። ግሩም ንግግር የማቅረብ ችሎታ ያላቸው ወንድሞች ወይም የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት በማስጀመር ረገድ የተዋጣላቸው እህቶች ለዚህ ችሎታቸው ምንጊዜም ቢሆን ይሖዋ እንዲወደስ ማድረግ ይኖርባቸዋል። w21.06 22 አን. 9-10