ሰኞ፣ ሚያዝያ 27
ጥበብ የባለቤቷን ሕይወት ጠብቃ [ታቆያለች]።—መክ. 7:12
ኢየሱስ “በአምላክ ዘንድ . . . ሀብታም” ሳንሆን ቁሳዊ ነገሮችን ማከማቸት ምን ያህል ሞኝነት እንደሆነ የሚያሳይ ምሳሌ ተናግሯል። (ሉቃስ 12:16-21) ነገ የሚያመጣውን ማንም አያውቅም። (ምሳሌ 23:4, 5፤ ያዕ. 4:13-15) የክርስቶስ ተከታዮች በመሆናችን ብቻ ሊገጥመን የሚችል ተፈታታኝ ሁኔታም አለ። ኢየሱስ እንደተናገረው የእሱ ደቀ መዛሙርት ለመሆን ስንል ካስፈለገ ንብረታችንን ሁሉ ‘ለመተው’ ዝግጁ መሆን አለብን። (ሉቃስ 14:33 ግርጌ) በመጀመሪያው መቶ ዘመን በይሁዳ የነበሩት ክርስቲያኖች እንዲህ ዓይነት እጦት ሲገጥማቸው ሁኔታውን በደስታ ተቀብለውታል። (ዕብ. 10:34) ዛሬ ያሉ ብዙ ወንድሞችም ለአንድ የፖለቲካ ሥርዓት ድጋፍ ላለመስጠት ሲሉ ቁሳዊ ነገሮችን መሥዋዕት አድርገዋል። (ራእይ 13:16, 17) እንዲህ ያለ አቋም ለመውሰድ የረዳቸው ምንድን ነው? ይሖዋ “ፈጽሞ አልተውህም፤ በምንም ዓይነት አልጥልህም” በማለት በገባው ቃል ላይ ሙሉ እምነት ማሳደራቸው ነው። (ዕብ. 13:5) እንግዲያው ለወደፊቱ ጊዜ ጥሩ ዕቅድ ማውጣታችን ተገቢ ነው፤ ያልተጠበቁ ሁኔታዎች ቢያጋጥሙን ደግሞ ይሖዋ ምንጊዜም እንደሚደግፈን መተማመን አለብን። w25.03 29 አን. 13-14
ማክሰኞ፣ ሚያዝያ 28
ስለ ክርስቶስ ከተማርነው መሠረታዊ ትምህርት አልፈን ስለሄድን ወደ ጉልምስና ለመድረስ እንጣጣር፤ መሠረትን ደግመን አንመሥርት።—ዕብ. 6:1
ይሖዋ በራሳችን ጥረት ብቻ ጉልምስና ደረጃ ላይ እንድንደርስ አይጠብቅብንም። በክርስቲያን ጉባኤ ውስጥ እረኞችና አስተማሪዎች ሆነው የሚያገለግሉት ወንድሞች በመንፈሳዊ “ሙሉ ሰው ወደ መሆን ይኸውም እንደ ክርስቶስ የተሟላ የጉልምስና ደረጃ ላይ” እንድንደርስ እኛን ለመርዳት ዝግጁ ናቸው። (ኤፌ. 4:11-13) ከዚህም ሌላ ይሖዋ ቅዱስ መንፈሱን በመስጠት “የክርስቶስ አስተሳሰብ” እንዲኖረን ይረዳናል። (1 ቆሮ. 2:14-16) በተጨማሪም አምላክ በመንፈስ መሪነት አራቱ ወንጌሎች እንዲጻፉልን አድርጓል፤ እነዚህ ወንጌሎች ኢየሱስ ምድር ላይ ሳለ አስተሳሰቡ፣ አነጋገሩና ድርጊቱ ምን ይመስል እንደነበር ያስተምሩናል። የኢየሱስን አስተሳሰብና ምግባር በመኮረጅ ክርስቲያናዊ ጉልምስና ላይ የመድረስ ግባችንን ማሳካት እንችላለን። ሆኖም ወደ ጉልምስና ደረጃ ለመድረስ “ስለ ክርስቶስ ከተማርነው መሠረታዊ ትምህርት” ማለትም መሠረታዊ ከሆኑት የክርስትና ትምህርቶች አልፈን መሄድ ይኖርብናል። w24.04 4-5 አን. 11-12
ረቡዕ፣ ሚያዝያ 29
የማመዛዘን ችሎታ ምንጊዜም ይጠብቅሃል፤ ጥልቅ ግንዛቤም ይጋርድሃል።—ምሳሌ 2:11
በየዕለቱ ውሳኔዎችን ማድረግ ያስፈልገናል። አንዳንዶቹን ውሳኔዎች ማድረግ ቀላል ነው፤ ለምሳሌ ‘ቁርስ ምን ልብላ’ ወይም ‘ስንት ሰዓት ልተኛ’ የሚለውን መወሰን ቀላል ነው። አንዳንዶቹን ውሳኔዎች ማድረግ ግን ከባድ ሊሆን ይችላል። እነዚህ ውሳኔዎች በጤንነታችን፣ በደስታችን፣ በወዳጅ ዘመዶቻችን ወይም በአምልኳችን ላይ ተጽዕኖ ሊያሳድሩ ይችላሉ። እኛንም ሆነ ቤተሰቦቻችንን የሚጠቅሙ ውሳኔዎችን ማድረግ እንፈልጋለን። ከሁሉ በላይ ደግሞ ውሳኔዎቻችን ይሖዋን የሚያስደስቱ እንዲሆኑ እንፈልጋለን። (ሮም 12:1, 2) ጥሩ ውሳኔ ለማድረግ የሚረዳህ አንዱ ወሳኝ እርምጃ የተሟላ መረጃ ማግኘት ነው። ለምን? ለምሳሌ አንድ ታማሚ ያጋጠመውን ከባድ የጤና ችግር አስመልክቶ ሐኪሙን አማከረ እንበል። ሐኪሙ በመጀመሪያ ታማሚውን ሳይመረምረው ወይም ጥያቄዎችን ሳይጠይቀው ምን ዓይነት ሕክምና እንደሚሰጠው ይወስናል? እንዲህ እንደማያደርግ የታወቀ ነው። አንተም በመጀመሪያ ከጉዳዩ ጋር የተያያዙ መረጃዎችን ለማግኘት ጥረት ካደረግክ ጥሩ ውሳኔ ማድረግ ትችላለህ። w25.01 14 አን. 1-3