ረቡዕ፣ መጋቢት 4
አምላክ በደግነቱ ወደ ንስሐ ሊመራህ እየሞከረ [ነው]።—ሮም 2:4
የጠርሴሱ ሳኦል የክርስቶስን ውድ ተከታዮች ክፉኛ ያሳድድ ነበር። አብዛኞቹ ክርስቲያኖች፣ ሳኦል ንስሐ ሊገባ እንደማይችል አስበው መሆን አለበት። ይሁንና የኢየሱስ አመለካከት እንዲህ ካለው የተሳሳተ ሰብዓዊ አስተሳሰብ በእጅጉ የላቀ ነው። እሱና አባቱ፣ ሳኦል መልካም ባሕርያት እንዳሉት ተመልክተዋል። ኢየሱስ ‘ይህ ሰው ለእኔ የተመረጠ ዕቃ ነው’ ብሏል። (ሥራ 9:15) እንዲያውም ኢየሱስ ሳኦልን ወደ ንስሐ ለመምራት ሲል ተአምር ፈጽሟል። (ሥራ 7:58–8:3፤ 9:1-9, 17-20) ሳኦል ክርስቲያን ከሆነና ሐዋርያው ጳውሎስ ተብሎ መጠራት ከጀመረ በኋላ፣ ለተደረገለት ደግነትና ምሕረት አመስጋኝነቱን በተደጋጋሚ ገልጿል። (1 ጢሞ. 1:12-15) ጳውሎስ በቆሮንቶስ በሚገኘው የክርስቲያን ጉባኤ ውስጥ የፆታ ብልግና እንደተፈጸመ ሲሰማ ጉዳዩን የያዘው እንዴት ነው? ጉዳዩን የያዘበት መንገድ ስለ ይሖዋ ፍቅራዊ ተግሣጽ እንዲሁም ምሕረት ማሳየት ስላለው አስፈላጊነት ብዙ ትምህርት ይሰጠናል። w24.08 13 አን. 15-16
ሐሙስ፣ መጋቢት 5
የአምላክ ልጅ የተገለጠው የዲያብሎስን ሥራ ለማፍረስ ነው።—1 ዮሐ. 3:8
ላለፉት መቶ ዘመናት ይሖዋ ኃጢአተኛ የሆኑ የሰው ልጆች ወደ እሱ መቅረብ የሚችሉት እንዴት እንደሆነ ደረጃ በደረጃ ግልጽ አድርጓል። በኤደን ዓመፅ ከተቀሰቀሰ በኋላ በይሖዋ ላይ እምነት የጣለው የመጀመሪያው ሰው የአዳምና የሔዋን ሁለተኛ ልጅ የሆነው አቤል ነው። አቤል ይሖዋን ስለሚወደው እንዲሁም እሱን ማስደሰትና ወደ እሱ መቅረብ ስለሚፈልግ መሥዋዕት አቀረበ። አቤል እረኛ ስለነበር ከጠቦቶቹ የተወሰኑትን አርዶ ለይሖዋ አቀረበ። በዚህ ጊዜ ይሖዋ ምን ተሰማው? “አቤልንና ያቀረበውን መባ በጥሩ ፊት [ተመለከተ]።” (ዘፍ. 4:4) ይሖዋ እሱን የሚወዱና በእሱ የሚታመኑ ሰዎች ያቀረቧቸውን ሌሎች መሥዋዕቶችም በሞገስ ዓይን ተመልክቷል፤ ለምሳሌ ኖኅ ያቀረበውን መሥዋዕት ተቀብሏል። (ዘፍ. 8:20, 21) ይሖዋ እንዲህ ያሉ መሥዋዕቶችን በመቀበል ኃጢአተኛ የሆኑ የሰው ልጆች የእሱን ሞገስ ማግኘትና ወደ እሱ መቅረብ እንደሚችሉ አሳይቷል። w24.08 3 አን. 5-6
ዓርብ፣ መጋቢት 6
እግሮቼ ከመንገድ ሊወጡ ተቃርበው ነበር፤ አዳልጦኝ ልወድቅ ምንም አልቀረኝም።—መዝ. 73:2
የፍትሕ መጓደል ሲያጋጥመን ስሜታችን በጥልቅ ሊጎዳና ልናዝን እንችላለን። (መክ. 7:7) እንደ ኢዮብና ዕንባቆም ያሉ ታማኝ የይሖዋ አገልጋዮችም እንደዚህ ተሰምቷቸው ነበር። (ኢዮብ 6:2, 3፤ ዕን. 1:1-3) እንዲህ ዓይነት ስሜት የሚሰማን መሆኑ የሚጠበቅ ነገር ቢሆንም የምንሰጠውን ምላሽ በተመለከተ ልንጠነቀቅ ይገባል፤ አለዚያ የሞኝነት ድርጊት ልንፈጽምና ሁኔታውን ልናባብሰው እንችላለን። ኢፍትሐዊ ድርጊት የሚፈጽሙ ሰዎች ለድርጊታቸው ምንም ቅጣት እንዳልተቀበሉ ሲሰማን ትክክል የሆነውን ነገር ማድረግ ጥቅም ያለው መሆኑን ልንጠራጠር እንችላለን። መዝሙራዊው፣ ክፉዎች ጻድቃንን ቢበድሉም እንኳ በሕይወታቸው ስኬታማ እንደሆኑ ተሰምቶት ነበር። “ክፉዎች እንደዚህ ናቸው፤ ሁልጊዜ ሳይጨናነቁ ይኖራሉ” ብሏል። (መዝ. 73:12) በተጨማሪም በዙሪያው የሚያየው የፍትሕ መጓደል በጣም ስላሳዘነው ይሖዋን ማገልገል ጥቅም ያለው መሆኑን መጠራጠር ጀምሮ ነበር። እንዲህ ብሏል፦ “ይህን ለመረዳት በሞከርኩ ጊዜ፣ የሚያስጨንቅ ሆነብኝ።”—መዝ. 73:14, 16፤ w24.11 3 አን. 5-7