ረቡዕ፣ ግንቦት 13
ይህ ሰው . . . ስለ ኃጢአት ለሁልጊዜ የሚሆን አንድ መሥዋዕት [አቅርቧል]።—ዕብ. 10:12
ኢየሱስ የኃጢአት ሸክም ለተጫናቸው ሰዎች ለየት ያለ ትኩረት ይሰጥ ነበር፤ ተከታዮቹ እንዲሆኑም ጋብዟቸዋል። በሰው ልጆች ላይ ለሚደርሰው መከራ ሁሉ ዋነኛው መንስኤ ኃጢአት እንደሆነ ያውቅ ነበር። በመሆኑም በኃጢአተኝነታቸው የሚታወቁ ሰዎችን ለመርዳት ጥረት አድርጓል። ሁኔታውን በምሳሌ ሲያስረዳ “ሐኪም የሚያስፈልጋቸው ሕመምተኞች እንጂ ጤነኞች አይደሉም” ብሏል። አክሎም እንዲህ አለ፦ “እኔ የመጣሁት ጻድቃንን ሳይሆን ኃጢአተኞችን ልጠራ ነው።” (ማቴ. 9:12, 13) ደግሞም ያደረገው ይህንኑ ነው። እግሩን በእንባዋ ያጠበችውን ሴት በርኅራኄ አነጋግሯታል፤ ኃጢአቷንም ይቅር ብሎላታል። (ሉቃስ 7:37-50) በውኃ ጉድጓዱ አጠገብ የነበረችው ሳምራዊት ሴት ሥነ ምግባር የጎደለው ሕይወት እንደምትመራ ቢያውቅም እንኳ ወሳኝ እውነቶችን አስተምሯታል። (ዮሐ. 4:7, 17-19, 25, 26) እንዲያውም አምላክ የኃጢአት የመጨረሻ ውጤት የሆነውን ሞትን እንዲቀለብስ ለኢየሱስ ኃይል ሰጥቶታል። እንዴት? ኢየሱስ ልጅ አዋቂ፣ ወንድ ሴት ሳይል ሰዎችን ከሞት አስነስቷል።—ማቴ. 11:5፤ w24.08 4 አን. 9-10
ሐሙስ፣ ግንቦት 14
በዓለም ላይ በጽድቅ፣ በሕዝቦችም ላይ በታማኝነት ይፈርዳል።—መዝ. 96:13
ይሖዋ በቅርቡ ስሙን የሚያስከብረው እንዴት ነው? በሚያስተላልፋቸው ፍርዶች አማካኝነት ነው። በቅርቡ፣ በስሙ ላይ ነቀፋ ያመጣችውን ታላቂቱ ባቢሎንን ያጠፋታል። (ራእይ 17:5, 16፤ 19:1, 2) የታላቂቱ ባቢሎንን ጥፋት የተመለከቱ አንዳንድ ሰዎች አብረውን በእውነተኛው አምልኮ መካፈል ይጀምሩ ይሆናል። በመጨረሻም፣ ይሖዋ በአርማጌዶን መላውን የሰይጣን ሥርዓት ያጠፋዋል፤ እሱን የሚቃወሙትንና ስሙን የሚሰድቡትን ሁሉ ይደመስሳል። የሚወዱትን፣ የሚታዘዙትንና ለእሱ ክብር በመስጠታቸው የሚኮሩትን ደግሞ ያድናቸዋል። (ማር. 8:38፤ 2 ተሰ. 1:6-10) የክርስቶስ የሺህ ዓመት ግዛት ሲያበቃ ከሚኖረው የመጨረሻ ፈተና በኋላ ይሖዋ ስሙን ሙሉ በሙሉ ያስቀድሳል። (ራእይ 20:7-10) በዚያ ጊዜ “ውኃ ባሕርን እንደሚሸፍን፣ ምድርም የይሖዋን ክብር በማወቅ ትሞላለች።” (ዕን. 2:14) በምድር ላይ ያለ ሰው ሁሉ ለስሙ የሚገባውን ክብር ለይሖዋ በሚሰጥበት ጊዜ መገኘት ምንኛ ያስደስታል! w25.01 7 አን. 15-16
ዓርብ፣ ግንቦት 15
ተግሣጽ የምትቀበሉበት አንዱ መንገድ ይህ ስለሆነ መከራ ሲደርስባችሁ መጽናት ያስፈልጋችኋል።—ዕብ. 12:7
ዕብራውያን ክርስቲያኖች የሚያጋጥማቸውን ተቃውሞ በጽናት ለመቋቋም ምን ሊረዳቸው ይችላል? ሐዋርያው ጳውሎስ ለሚያጋጥሟቸው ፈተናዎች ትክክለኛው አመለካከት ሊኖራቸው እንደሚገባ ተገንዝቦ ነበር። በመሆኑም አምላክ አንድ ክርስቲያን ሥልጠና እንዲያገኝ ሲል የእምነት ፈተናዎች እንዲደርሱበት ሊፈቅድ እንደሚችል ጳውሎስ አብራራላቸው። እንዲህ ያለው ሥልጠና ግለሰቡ ወሳኝ ክርስቲያናዊ ባሕርያትን እንዲያዳብርና እንዲያሻሽል ይረዳዋል። ዕብራውያን ክርስቲያኖች ፈተናዎቹ በሚያስገኙት ውጤት ላይ ማተኮራቸው መጽናት ቀላል እንዲሆንላቸው ያደርጋል። (ዕብ. 12:11) ዕብራውያን ክርስቲያኖች ፈተናዎችን በጽናት ለመቋቋም ይበልጥ ቁርጠኛ እንዲሆኑ ጳውሎስ አሳስቧቸዋል። ደግሞም ስደትን በጽናት ስለመቋቋም ከተነሳ ጳውሎስ ብዙ የሚያውቀው ነገር አለ። ቀደም ሲል ክርስቲያኖችን ያሳድድ ስለነበር የሚጋፈጡት ስደት ምን ያህል ከባድ እንደሆነ ያውቃል። ስደትን በጽናት መቋቋም የሚቻለው እንዴት እንደሆነም ያውቃል። ምክንያቱም ክርስቲያን ከሆነ በኋላ የተለያየ ዓይነት ተቃውሞ ደርሶበታል።—2 ቆሮ. 11:23-25፤ w24.09 12 አን. 16-17