-
እድገትህ በግልጽ እንዲታይ አድርግመጠበቂያ ግንብ—2009 | ታኅሣሥ 15
-
-
6 ጳውሎስ፣ ለጢሞቴዎስ “ታማኞች ለሆኑት በንግግር፣ በምግባር፣ በፍቅር፣ በእምነትና በንጽሕና አርዓያ” እንዲሆን ጽፎለታል። አክሎም “እድገትህ በሁሉም ሰዎች ዘንድ በግልጽ እንዲታይ በእነዚህ ነገሮች ላይ አሰላስል፤ እንዲሁም ትኩረትህ ሙሉ በሙሉ በእነዚህ ነገሮች ላይ ያረፈ ይሁን” ብሎታል። (1 ጢሞ. 4:12, 15) ጢሞቴዎስ እድገት ማድረግ የነበረበት ከኃላፊነት ቦታ አንጻር ሳይሆን መንፈሳዊ ባሕርያትን ከማዳበር ጋር በተያያዘ ነበር። ደግሞም እያንዳንዱ ክርስቲያን ማሳየት ያለበት እንዲህ ያለ መንፈሳዊ እድገት ነው።
-
-
እድገትህ በግልጽ እንዲታይ አድርግመጠበቂያ ግንብ—2009 | ታኅሣሥ 15
-
-
በንግግር ረገድ አርዓያ መሆን
8. ንግግራችን በአምልኮታችን ላይ ምን ሊያስከትል ይችላል?
8 ጢሞቴዎስ አርዓያ ከሚሆንባቸው መንገዶች አንዱ በአነጋገሩ ነበር። እኛስ ከአነጋገር ጋር በተያያዘ እድገታችን በግልጽ እንዲታይ ማድረግ የምንችለው እንዴት ነው? ንግግራችን ስለ እኛ ማንነት የሚጠቁመው ብዙ ነገር አለ። ኢየሱስ “አንደበት የሚናገረው በልብ ውስጥ የሞላውን ነው” ብሎ መናገሩ የተገባ ነው። (ማቴ. 12:34) በተጨማሪም የኢየሱስ ወንድም የሆነው ያዕቆብ ንግግራችን በአምልኮታችን ላይ ሊያስከትል የሚችለውን ውጤት ተገንዝቦ ነበር። እንዲህ በማለት ጽፏል፦ “አንድ ሰው አምልኮቱን እያከናወነ እንዳለ የሚሰማው ቢሆንም እንኳ አንደበቱን የማይገታ ከሆነ ይህ ሰው የገዛ ልቡን እያታለለ ይኖራል፤ የዚህ ሰው አምልኮም ከንቱ ነው።”—ያዕ. 1:26
9. በአነጋገር ረገድ አርዓያ መሆን የምንችለው እንዴት ነው?
9 ንግግራችን በጉባኤ ውስጥ ለሚገኙ ወንድሞች በመንፈሳዊ ምን ያህል እድገት እንዳደረግን ይጠቁማቸዋል። በመሆኑም የጎለመሱ ክርስቲያኖች ወራዳ፣ አሉታዊ፣ ነቀፋ የሞላበት ወይም የሚጎዳ ነገር ከመናገር ይልቅ በንግግራቸው ሌሎችን ለማነጽ፣ ለማበረታታትና ለማጽናናት ይጥራሉ። (ምሳሌ 12:18፤ ኤፌ. 4:29፤ 1 ጢሞ. 6:3-5, 20) የምንከተለውን የሥነ ምግባር አቋም እንዲሁም አምላክ ባወጣቸው የላቁ የሥነ ምግባር መሥፈርቶች መመራት የምንፈልገው ለምን እንደሆነ ሁልጊዜ ለሌሎች መናገራችን ለአምላክ ያደርን መሆናችንን ያሳያል። (ሮም 1:15, 16) ቅን ልብ ያላቸው ሰዎች የመናገር ችሎታችንን ጥሩ አድርገን እንደምንጠቀምበት ማስተዋላቸው አይቀርም፤ ይህ ደግሞ የእኛን አርዓያ እንዲከተሉ ሊያነሳሳቸው ይችላል።—ፊልጵ. 4:8, 9
በምግባርና በንጽሕና አርዓያ መሆን
10. መንፈሳዊ እድገት ለማድረግ ግብዝነት የሌለበት እምነት ማዳበራችን አስፈላጊ የሆነው ለምንድን ነው?
10 አንድ ክርስቲያን ጥሩ አርዓያ መሆን የሚጠበቅበት በአነጋገሩ ብቻ አይደለም። የሚናገረው ነገር ትክክል ቢሆንም በተግባር ካልተደገፈ ግብዝ ያደርገዋል። ጳውሎስ የፈሪሳውያንን ግብዝነትም ሆነ ይህ አካሄዳቸው ሊያስከትል የሚችለውን መዘዝ በሚገባ ያውቅ ነበር። በመሆኑም ጢሞቴዎስን እንዲህ ካለው ግብዝነት እንዲርቅ እንዲሁም ያልሆነውን ሆኖ ለመታየት ከመሞከር እንዲቆጠብ በተደጋጋሚ ጊዜ አስጠንቅቆታል። (1 ጢሞ. 1:5፤ 4:1, 2) ይሁንና ጢሞቴዎስ ግብዝ አልነበረም። ጳውሎስ ለጢሞቴዎስ በላከው በሁለተኛው ደብዳቤ ላይ “በአንተ ውስጥ ያለውን ምንም ግብዝነት የሌለበት እምነት አስታውሳለሁ” ሲል ጽፏል። (2 ጢሞ. 1:5) እንደዚያም ሆኖ ጢሞቴዎስ ግብዝ ክርስቲያን አለመሆኑን ለሌሎች በግልጽ ማሳየት ነበረበት። በምግባሩ አርዓያ ሆኖ መገኘት ይጠበቅበት ነበር።
11 ጳውሎስ ቁሳዊ ሀብትን አስመልክቶ ለጢሞቴዎስ ምን ጽፎለታል?
11 ጳውሎስ ለጢሞቴዎስ በጻፋቸው ሁለት ደብዳቤዎች ላይ ምግባርን በሚመለከት ከተለያየ አቅጣጫ ምክር ሰጥቶታል። ለምሳሌ ያህል፣ ጢሞቴዎስ ቁሳዊ ሀብትን ከማሳደድ መቆጠብ ነበረበት። ጳውሎስ እንዲህ ሲል ጽፎለታል፦ “የገንዘብ ፍቅር የብዙ ዓይነት ጎጂ ነገሮች ሥር ነው፤ አንዳንዶች በዚህ ፍቅር ተጠምደው ከእምነት ጎዳና ስተው ወጥተዋል፤ እንዲሁም ሁለንተናቸውን በብዙ ሥቃይ ወግተዋል።” (1 ጢሞ. 6:10) አንድ ሰው ቁሳዊ ሀብትን መውደዱ በመንፈሳዊ ችግር እንዳለበት ይጠቁማል። ከዚህ በተቃራኒ ግን ባላቸው “ምግብ እንዲሁም ልብስና መጠለያ” ረክተው ቀላል ሕይወት የሚመሩ ክርስቲያኖች መንፈሳዊ እድገታቸው በግልጽ ይታያል።—1 ጢሞ. 6:6-8፤ ፊልጵ. 4:11-13
12. በዕለት ተዕለት ሕይወታችን እድገታችን በግልጽ እንዲታይ ማድረግ የምንችለው እንዴት ነው?
12 ጳውሎስ ክርስቲያን ሴቶች “በልከኝነትና በማስተዋል ሥርዓታማ በሆነ ልብስ ራሳቸውን [ማስዋባቸው]” ምን ያህል አስፈላጊ እንደሆነ ለጢሞቴዎስ ገልጾለታል። (1 ጢሞ. 2:9) በአለባበስና በአጋጌጥ ምርጫቸው ብሎም በሌሎች የሕይወታቸው ዘርፎች ልከኛ እንዲሁም አስተዋይ የሆኑ ሴቶች ግሩም ምሳሌ ይሆናሉ። (1 ጢሞ. 3:11) ይህ መሠረታዊ ሥርዓት ለክርስቲያን ወንዶችም ይሠራል። ጳውሎስ የበላይ ተመልካቾች ‘በልማዶቻቸው ልከኛ እንዲሆኑ፣ ጤናማ አስተሳሰብ እንዲኖራቸውና ሥርዓታማ እንዲሆኑ’ አሳስቧቸዋል። (1 ጢሞ. 3:2) እኛም በዕለት ተዕለት ሕይወታችን እነዚህን ባሕርያት ስናሳይ እድገታችን ለሁሉም ሰው በግልጽ ይታያል።
13. እንደ ጢሞቴዎስ ሁሉ እኛም በንጽሕና ረገድ አርዓያ መሆን የምንችለው እንዴት ነው?
13 ጢሞቴዎስ በንጽሕና ረገድም አርዓያ መሆን ነበረበት። ጳውሎስ ንጽሕና የሚለውን ቃል የተጠቀመው ምግባር ከሚገለጽባቸው መንገዶች አንዱን በተለይም የፆታ ሥነ ምግባርን በተዘዋዋሪ ለማመልከት ነበር። ጢሞቴዎስ በተለይ ከሴቶች ጋር ባለው ግንኙነት ረገድ የማይነቀፍ ምግባር ማሳየት ይጠበቅበት ነበር። ‘አሮጊቶችን እንደ እናቶች፣ ወጣት ሴቶችን ደግሞ እንደ እህቶች አድርጎ በፍጹም ንጽሕና’ መያዝ ነበረበት። (1 ጢሞ. 4:12፤ 5:2) አንድ ሰው አንድ ዓይነት የሥነ ምግባር ብልግናን ማንም ሳያየው እንደፈጸመ ቢሰማውም እንኳ ድርጊቱ በአምላክ ፊት የተሰወረ አይደለም፤ ይዋል ይደር እንጂ በሰዎችም ዘንድ መታወቁ አይቀርም። በተመሳሳይም አንድ ክርስቲያን የሚሠራቸው መልካም ሥራዎች ተደብቀው ሊቀሩ አይችሉም። (1 ጢሞ. 5:24, 25) በጉባኤ ውስጥ ያሉ ሁሉም ክርስቲያኖች በምግባርና በንጽሕና ረገድ እድገታቸው በግልጽ እንዲታይ የማድረግ አጋጣሚ አላቸው።
ፍቅርና እምነት አስፈላጊ ነው
14. ቅዱሳን መጻሕፍት እርስ በርስ የመዋደድን አስፈላጊነት ጎላ አድርገው የሚገልጹት እንዴት ነው?
14 የእውነተኛ ክርስትና ዋነኛ መታወቂያው ፍቅር ነው። ኢየሱስ “በመካከላችሁ ፍቅር ካለ ሰዎች ሁሉ ደቀ መዛሙርቴ እንደሆናችሁ በዚህ ያውቃሉ” በማለት ለደቀ መዛሙርቱ ነግሯቸዋል። (ዮሐ. 13:35) እንዲህ ያለውን ፍቅር ማሳየት የምንችለው እንዴት ነው? የአምላክ ቃል ‘እርስ በርስ በፍቅር’ እንድንቻቻል፣ ‘አንዳችን ለሌላው ደጎችና ከአንጀት የምንራራ እንድንሆን፣ እርስ በርሳችን በነፃ ይቅር እንድንባባል’ እንዲሁም እንግዳ ተቀባይ እንድንሆን ይመክረናል። (ኤፌ. 4:2, 32፤ ዕብ. 13:1, 2) ሐዋርያው ጳውሎስ “በወንድማማች ፍቅር እርስ በርሳችሁ ከልብ ተዋደዱ” ሲል ጽፏል።—ሮም 12:10
15. ሁሉም ክርስቲያኖች በተለይም ክርስቲያን የበላይ ተመልካቾች ፍቅር ማሳየታቸው በጣም አስፈላጊ የሆነው ለምንድን ነው?
15 ጢሞቴዎስ የእምነት ባልንጀሮቹን በኃይል ወይም ደግነት በጎደለው መንገድ ቢይዛቸው ኖሮ ይህ ድርጊቱ አስተማሪና የበላይ ተመልካች ሆኖ የሚያከናውነው መልካም ተግባር ጎልቶ እንዳይታይ ያደርግበት ነበር። (1 ቆሮንቶስ 13:1-3ን አንብብ።) በሌላ በኩል ግን ጢሞቴዎስ ለወንድሞቹ ከልብ የመነጨ ፍቅር ማሳየቱ እንዲሁም እነሱን በእንግድነት መቀበሉና ለእነሱ መልካም ማድረጉ መንፈሳዊ እድገቱ ጎልቶ እንዲታይ እንደሚያደርግ ምንም ጥርጥር የለውም። በመሆኑም ሐዋርያው ጳውሎስ ለጢሞቴዎስ በጻፈው ደብዳቤ ላይ አርዓያ መሆን ከሚጠበቅበት ባሕርያት መካከል ፍቅርን መጥቀሱ ተገቢ ነበር።
16. ጢሞቴዎስ ጠንካራ እምነት ማሳየት የነበረበት ለምንድን ነው?
16 ጢሞቴዎስ በኤፌሶን በቆየባቸው ጊዜያት እምነቱ ተፈትኖ ነበር። አንዳንዶች ከክርስትና እውነቶች ጋር የሚጋጩ መሠረተ ትምህርቶችን ያስፋፉ ነበር። ሌሎች ደግሞ ‘የፈጠራ ወሬዎችን’ ወይም ለጉባኤው መንፈሳዊነት ምንም የማይፈይዱ እርባና ቢስ ሐሳቦችን ያሰራጩ ነበር። (1 ጢሞቴዎስ 1:3, 4ን አንብብ።) ጳውሎስ እንዲህ ያሉ ግለሰቦችን ‘በትዕቢት የተወጠሩና ምንም የማያስተውሉ ይሁንና ስለ ቃላት ጥያቄ የማንሳትና የመከራከር አባዜ የተጠናወታቸው’ በማለት ገልጿቸዋል። (1 ጢሞ. 6:3, 4) ጢሞቴዎስ ወደ ጉባኤው ሰርገው በገቡት በእነዚህ ጎጂ ሐሳቦች ላይ በማውጠንጠን መንፈሳዊነቱን አደጋ ላይ ይጥል ይሆን? በፍጹም! ምክንያቱም ጳውሎስ ‘መልካሙን የእምነት ተጋድሎ እንዲጋደል’ እንዲሁም “ቅዱስ የሆነውን ነገር ከሚጻረሩ ከንቱ ንግግሮችና በውሸት ‘እውቀት’ ተብለው ከሚጠሩ እርስ በርሳቸው ከሚቃረኑ ሐሳቦች” እንዲርቅ ጢሞቴዎስን አሳስቦት ነበር። (1 ጢሞ. 6:12, 20, 21) ጢሞቴዎስ፣ ጳውሎስ የሰጠውን ጥበብ ያዘለ ምክር እንደተከተለ ምንም ጥርጥር የለውም።—1 ቆሮ. 10:12
17. በዛሬው ጊዜ እምነታችን ሊፈተን የሚችለው እንዴት ነው?
17 የሚገርመው ነገር ጢሞቴዎስ “በኋለኞቹ ዘመናት አንዳንዶች ከመናፍስት ለሚመነጩ አሳሳች ቃሎችና የአጋንንት ትምህርቶች ጆሯቸውን በመስጠት ከእምነት [እንደሚወጡ]” ተነግሮት ነበር። (1 ጢሞ. 4:1) በኃላፊነት ቦታ ላይ የሚገኙ ግለሰቦችን ጨምሮ በጉባኤ ውስጥ ያሉ ክርስቲያኖች በሙሉ እንደ ጢሞቴዎስ ጠንካራና ጽኑ እምነት መያዛቸው አስፈላጊ ነው። ክህደትን በመቃወም ረገድ ጠንካራ አቋም በመያዝና ቁርጥ ያለ እርምጃ በመውሰድ እድገታችን በግልጽ እንዲታይ ማድረግ ብሎም በእምነት ለሌሎች አርዓያ መሆን እንችላለን።
-