ሰኞ፣ መጋቢት 30
የአምላክ ፍቅር . . . በዚህ መንገድ ተገልጧል።—1 ዮሐ. 4:9
ቤዛው በዋጋ የማይተመን ስጦታ ነው ቢባል እንደምትስማማ ምንም ጥርጥር የለውም! (2 ቆሮ. 9:15) ከይሖዋ ጋር የጠበቀ ወዳጅነት መመሥረት የቻልነው ኢየሱስ ሰብዓዊ ሕይወቱን መሥዋዕት አድርጎ ስለከፈለ ነው። የዘላለም ሕይወት ተስፋም አስገኝቶልናል። ይሖዋ በፍቅር ተነሳስቶ የቤዛውን ዝግጅት ስላደረገልን አመስጋኝ መሆናችን ምንኛ የተገባ ነው! (ሮም 5:8) ኢየሱስ አመስጋኝ ሆነን እንድንቀጥልና ቤዛውን አቅልለን እንዳንመለከት ሲል የሞቱን መታሰቢያ በዓል በየዓመቱ እንድናከብር አዞናል። (ሉቃስ 22:19, 20) በዚህ ዓመት የመታሰቢያው በዓል የሚከበረው ሐሙስ፣ ሚያዝያ 2, 2026 ነው። ሁላችንም ለመገኘት እንደምንፈልግ ጥርጥር የለውም። በመታሰቢያው በዓል ሰሞን ይሖዋና ልጁ ስላደረጉልን ነገር ጊዜ ወስደን ማሰላሰላችን በእጅጉ ይጠቅመናል። w25.01 20 አን. 1-2
የመታሰቢያው በዓል የመጽሐፍ ቅዱስ ንባብ፦ (ቀን ላይ የተከናወኑ ነገሮች፦ ኒሳን 10) ዮሐንስ 12:20-50
ማክሰኞ፣ መጋቢት 31
ከብር ይልቅ ተግሣጼን፣ ጥራት ካለውም ወርቅ ይልቅ እውቀትን ተቀበሉ።—ምሳሌ 8:10
ይሖዋ አምላክና ኢየሱስ ክርስቶስ ባደረጉልን ነገር ላይ ማሰላሰልህን ከቀጠልክ ለእኛ ስላላቸው ፍቅር ይበልጥ መማር ትችላለህ። ምናልባትም የመታሰቢያው በዓል በሚከበርበት ሰሞን አንዳንዶቹን የወንጌል መጻሕፍት በጥሞና ለማንበብ ጥረት ልታደርግ ትችላለህ። በአንድ ጊዜ ብዙ ምዕራፎችን ለማንበብ አትሞክር። ከዚህ ይልቅ፣ ረጋ ብለህ ይሖዋንና ኢየሱስን ለመውደድ የሚያነሳሱንን ተጨማሪ ምክንያቶች ለማግኘት ሞክር። በእውነት ውስጥ ለብዙ ዓመታት ቆይተህ ከሆነ ስለ ይሖዋ ፍትሕ፣ ስለ ፍቅሩ፣ ስለ ቤዛው ወይም እንደዚህ ስለመሳሰሉ የተለመዱ ርዕሰ ጉዳዮች አዲስ እውቀት ማግኘት የምትችል አይመስልህ ይሆናል። እንደ እውነቱ ከሆነ ግን ስለ እነዚህም ሆነ ስለ ሌሎች ርዕሰ ጉዳዮች ገና የማናውቀው ብዙ ነገር አለ። በጽሑፎቻችን ውስጥ ደግሞ ብዙ መረጃ ይገኛል፤ ስለዚህ ጽሑፎቻችንን ጥሩ አድርገህ ተጠቀምባቸው። w25.01 24-25 አን. 13-15
የመታሰቢያው በዓል የመጽሐፍ ቅዱስ ንባብ፦ (ቀን ላይ የተከናወኑ ነገሮች፦ ኒሳን 11) ሉቃስ 21:1-36
ረቡዕ፣ ሚያዝያ 1
የአባቴ ፈቃድ ወልድን የሚያውቅና በእሱ የሚያምን ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዲኖረው ነው።—ዮሐ. 6:40
ከኢየሱስ ሥጋና ደም ጥቅም ማግኘት ከፈለግን በቤዛው ማመን ያስፈልገናል። (ኤፌ. 1:7) ኢየሱስ “ሌሎች በጎች” በማለት የጠራቸው ሰዎች በዓመታዊው የጌታ ራት ወቅት ከቂጣውና ከወይን ጠጁ አይካፈሉም፤ መካፈልም የለባቸውም። (ዮሐ. 10:16) ያም ቢሆን ከኢየሱስ ሥጋና ደም ጥቅም ያገኛሉ። ይህን የሚያደርጉት እሱ ያቀረበው መሥዋዕት ባለው የመዋጀት ኃይል ላይ እምነት በማሳደር ነው። (ዮሐ. 6:53) በአንጻሩ ግን፣ ከቂጣውና ከወይን ጠጁ የሚካፈሉት ሰዎች የአዲሱ ቃል ኪዳን ክፍል እንደሆኑና የሰማያዊው መንግሥት ወራሾች ለመሆን እንደተመረጡ ያሳያሉ። ከዚህ እንደምንረዳው፣ ቅቡዓን ክርስቲያኖችም ሆንን የሌሎች በጎች ክፍል እምነት ማሳየት ይኖርብናል። የዘላለም ሕይወት ማግኘታችን የተመካው በዚህ ላይ ነው። w24.12 12 አን. 14፤ 13 አን. 16
የመታሰቢያው በዓል የመጽሐፍ ቅዱስ ንባብ፦ (ቀን ላይ የተከናወኑ ነገሮች፦ ኒሳን 12) ማቴዎስ 26:1-5, 14-16፤ ሉቃስ 22:1-6