ሰኞ፣ ሐምሌ 20
ከልክ በላይ በሐዘን እንዳይዋጥ በደግነት ይቅር ልትሉትና ልታጽናኑት ይገባል።—2 ቆሮ. 2:7
አንድ ግለሰብ እውነተኛ ንስሐ ከገባ በኋላ ሽማግሌዎቹ ወደ ጉባኤው እንዳይመለስ ቢከለክሉት ወይም ደግሞ ከተመለሰ በኋላ ጉባኤው ለእሱ ፍቅር ለማሳየት ፈቃደኛ ባይሆን ምን እንደሚከሰት ለማሰብ ሞክር። ግለሰቡ “ከልክ በላይ በሐዘን” ይዋጣል። ምንም ተስፋ እንደሌለው ሊሰማው ይችላል። ከአምላክ ጋር ያለውን ዝምድና ለማደስ ጥረት ማድረጉን ሊያቆምም ይችላል። ይህ ብቻ ሳይሆን፣ በጉባኤው ውስጥ ያሉ ሌሎች ወንድሞችና እህቶች ንስሐ የገባውን ኃጢአተኛ ይቅር ለማለት ፈቃደኛ ካልሆኑ እነሱ ራሳቸው ከአምላክ ጋር ያላቸውን ወዳጅነት ሊያበላሹ ይችላሉ። እንዲህ የምንለው ለምንድን ነው? ምክንያቱም ንስሐ ለገቡ ኃጢአተኞች ምሕረት የሚያሳየውን ይሖዋን ሳይሆን ጨካኝና ምሕረት የለሽ የሆነውን ሰይጣንን መምሰል ይሆንባቸዋል። እንዲህ ካደረጉ፣ ዲያብሎስ ግለሰቡን በመንፈሳዊ ለማጥፋት የሚጠቀምበት መሣሪያ ሊሆኑ ይችላሉ።—2 ቆሮ. 2:10, 11፤ ኤፌ. 4:27፤ w24.08 17 አን. 7, 10-11
ማክሰኞ፣ ሐምሌ 21
ወደ ላይ በወጣ ጊዜ [ሰዎችን] ስጦታ አድርጎ ሰጠ።—ኤፌ. 4:8
ክርስቶስ ኢየሱስ በሌላ መንገድ የሚያገለግሉ ‘ስጦታ የሆኑ ሰዎችንም’ ሰጥቷል። በኢየሩሳሌም የነበሩት ሽማግሌዎች በእሱ አመራር ሥር ሆነው ጳውሎስን፣ በርናባስንና ሌሎችን ተጓዥ የበላይ ተመልካቾች አድርገው ልከዋቸው ነበር። (ሥራ 11:22) ለምን? ዓላማው የጉባኤ አገልጋዮችና ሽማግሌዎች ከሚሾሙበት ምክንያት ጋር ተመሳሳይ ነው፦ ጉባኤዎችን ማነጽ። (ሥራ 15:40, 41) የወረዳ የበላይ ተመልካቾች ሁልጊዜ ጉዞ ላይ ናቸው። አንዳንዶቹ ከአንዱ ጉባኤ ወደ ሌላው ጉባኤ ለመሄድ በመቶዎች የሚቆጠሩ ኪሎ ሜትሮችን መጓዝ ያስፈልጋቸዋል። አንድ የወረዳ የበላይ ተመልካች በየሳምንቱ የተለያዩ ንግግሮችን ያቀርባል፤ እረኝነት ያደርጋል፤ እንዲሁም የአቅኚዎች ስብሰባ፣ የሽማግሌዎች ስብሰባና የስምሪት ስብሰባዎችን ይመራል። ንግግሮችን ይዘጋጃል፤ እንዲሁም የወረዳ ስብሰባዎችንና የክልል ስብሰባዎችን ያደራጃል። በአቅኚዎች ትምህርት ቤት ላይ ያስተምራል፤ በወረዳው ውስጥ ካሉ አቅኚዎች ጋር የሚደረገውን ልዩ ስብሰባ ያደራጃል፤ እንዲሁም ቅርንጫፍ ቢሮው የሚሰጠውን ሌሎች ኃላፊነቶች ይወጣል፤ እነዚህ ኃላፊነቶች አንዳንድ ጊዜ አስቸኳይ ሊሆኑ ይችላሉ። w24.10 21 አን. 12-13
ረቡዕ፣ ሐምሌ 22
በደላቸውን ይቅር እላለሁና፤ ኃጢአታቸውንም ከእንግዲህ አላስታውስም።—ኤር. 31:34
ነቢዩ ኤርምያስ፣ ይሖዋ በዛሬው የዕለት ጥቅስ ላይ ያለውን ሐሳብ እንደተናገረ ጽፏል። ሐዋርያው ጳውሎስም ይህን ሐሳብ በመጥቀስ “ኃጢአታቸውንም ከእንግዲህ ወዲህ አላስታውስም” ሲል ጽፏል። (ዕብ. 8:12) ይሁንና ይህ ሲባል ምን ማለት ነው? በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ “ማስታወስ” ወይም “ማሰብ” የሚለው ቃል አንድን ነገር ወደ አእምሮ ማምጣትን ብቻ አያመለክትም። ከዚህ ይልቅ እርምጃ መውሰድንም ያካትታል። ከኢየሱስ አጠገብ የተሰቀለው ወንጀለኛ “ኢየሱስ ሆይ፣ ወደ መንግሥትህ ስትመጣ አስበኝ” በማለት ጠይቆታል። (ሉቃስ 23:42, 43) ይህን ሲል፣ ኢየሱስ በዚያ ወቅት ስለ እሱ እንዲያስብ መጠየቁ ብቻ አይደለም። ኢየሱስ የሰጠው ምላሽ፣ ወንጀለኛውን በማስነሳት እርምጃ እንደሚወስድ ይጠቁማል። ስለዚህ ይሖዋ ኃጢአታችንን አያስታውስም ሲባል በኃጢአታችን ምክንያት እርምጃ አይወስድብንም ማለት ነው። አንድን ኃጢአት ይቅር ካለን በኋላ ወደፊት በዚያ ኃጢአት የተነሳ አይቀጣንም። w25.02 10-11 አን. 14-15