ሐሙስ፣ መጋቢት 30
ሌሎች በጎች አሉኝ።—ዮሐ. 10:16
ሌሎች በጎች በመታሰቢያው በዓል ላይ ታዳሚ ሆነው በመገኘታቸው ደስተኛ ናቸው፤ በተስፋቸው ላይ ለማሰላሰልም አጋጣሚ ያገኛሉ። የመታሰቢያው በዓል በሚከበርበት ዕለት የሚሰጠውን ንግግር ለማዳመጥ ይጓጓሉ፤ ምክንያቱም ንግግሩ በአብዛኛው የሚያተኩረው ክርስቶስ እና 144,000 ተባባሪ ገዢዎቹ በሺህ ዓመት ግዛቱ ወቅት ለታማኝ የሰው ልጆች በሚያደርጉት ነገር ላይ ነው። እነዚህ ተባባሪ ገዢዎች በንጉሣቸው በኢየሱስ ክርስቶስ አመራር ሥር ሆነው ምድር ገነት እንድትሆን እንዲሁም የሰው ዘር ፍጽምና ደረጃ ላይ እንዲደርስ በሚከናወነው ሥራ ትልቅ እገዛ ያበረክታሉ። በሚሊዮኖች የሚቆጠሩት የመታሰቢያው በዓል ታዳሚዎች እንደ ኢሳይያስ 35:5, 6፤ 65:21-23 እና ራእይ 21:3, 4 ባሉ የመጽሐፍ ቅዱስ ትንቢቶች ፍጻሜ ላይ በማሰላሰል ምን ያህል እንደሚደሰቱ አስቡት። ከሚወዷቸው ሰዎች ጋር በአዲሱ ዓለም ውስጥ የሚኖራቸውን ሕይወት በዓይነ ሕሊናቸው መሣላቸው የወደፊቱ ተስፋቸው ይበልጥ እውን እንዲሆንላቸው ያደርጋል፤ ይሖዋን እስከ መጨረሻው ለማገልገል ያላቸው ቁርጠኝነትም ይጠናከራል።—ማቴ. 24:13፤ ገላ. 6:9፤ w22.01 21 አን. 5-7
የመታሰቢያው በዓል የመጽሐፍ ቅዱስ ንባብ፦ (ፀሐይ ከጠለቀች በኋላ የተከናወኑ ነገሮች፦ ኒሳን 9) ማቴዎስ 26:6-13
ዓርብ፣ መጋቢት 31
የሰው ልጅ . . . የመጣው . . . በብዙ ሰዎች ምትክ ሕይወቱን ቤዛ አድርጎ ለመስጠት [ነው]።—ማር. 10:45
ቤዛው ምንድን ነው? አዳም ያጣውን ነገር ለማስመለስ ኢየሱስ የከፈለው ዋጋ ነው። (1 ቆሮ. 15:22) ቤዛው የሚያስፈልገን ለምንድን ነው? በሙሴ ሕግ ውስጥ በተገለጸው የይሖዋ የፍትሕ መሥፈርት መሠረት ሕይወት ስለ ሕይወት መከፈል ስላለበት ነው። (ዘፀ. 21:23, 24) አዳም ያጣው ፍጹም ሰብዓዊ ሕይወቱን ነው። ስለዚህ በአምላክ ሕግ መሠረት ፍትሕ እንዲፈጸም ኢየሱስ ፍጹም ሰብዓዊ ሕይወቱን መሥዋዕት አደረገ። (ሮም 5:17) በመሆኑም በቤዛው ለሚያምኑ ሁሉ “የዘላለም አባት” ሆነ። (ኢሳ. 9:6፤ ሮም 3:23, 24) ኢየሱስ በሰማይ ላለው አባቱና ለእኛ ታላቅ ፍቅር ስላለው ሕይወቱን መሥዋዕት አድርጎ ለማቅረብ ፈቃደኛ ሆኗል። (ዮሐ. 14:31፤ 15:13) እንዲህ ዓይነት ፍቅር ያለው መሆኑ እስከ ሞት ድረስ ታማኝ ለመሆን እንዲሁም የአባቱን ፈቃድ ለመፈጸም አነሳስቶታል። ኢየሱስ ይህን ማድረጉ ይሖዋ መጀመሪያ ላይ ለሰው ልጆችና ለምድር የነበረው ዓላማ እንዲፈጸም ያደርጋል። w21.04 14 አን. 2-3
የመታሰቢያው በዓል የመጽሐፍ ቅዱስ ንባብ፦ (ቀን ላይ የተከናወኑ ነገሮች፦ ኒሳን 9) ማቴዎስ 21:1-11, 14-17
ቅዳሜ፣ ሚያዝያ 1
አምላክ ዓለምን እጅግ ከመውደዱ የተነሳ . . . አንድያ ልጁን ሰጥቷል።—ዮሐ. 3:16
ኢየሱስ ለእኛ ሲል ሕይወቱን በፈቃደኝነት መስጠቱ ታላቅ የፍቅር መገለጫ ነው። (ዮሐ. 15:13) ይሖዋ እና ኢየሱስ የዋሉልንን ውለታ መቼም ቢሆን መክፈል አንችልም። ሆኖም በዕለት ተዕለት ሕይወታችን አመስጋኝነታችንን ማሳየት እንችላለን። (ቆላ. 3:15) ቅቡዓኑ አስደናቂ ተስፋ እንዲያገኙ መንገድ ስለከፈተላቸው ቤዛውን ከፍ አድርገው ይመለከቱታል። (ማቴ. 20:28) በክርስቶስ መሥዋዕት ላይ ያላቸውን እምነት መሠረት በማድረግ ይሖዋ ጻድቃን ናችሁ ብሏቸዋል፤ ልጆቹ አድርጎም ወስዷቸዋል። (ሮም 5:1፤ 8:15-17, 23) ሌሎች በጎችም ለቤዛው አድናቆት አላቸው። በፈሰሰው የክርስቶስ ደም ላይ እምነት ስላላቸው በአምላክ ፊት ንጹሕ አቋም አግኝተዋል፤ እንዲሁም “ታላቁን መከራ አልፈው” በሕይወት የመኖር ተስፋ አላቸው። (ራእይ 7:13-15) ሁለቱም ቡድኖች ለቤዛው ያላቸውን አድናቆት ማሳየት የሚችሉበት አንዱ መንገድ በየዓመቱ በመታሰቢያው በዓል ላይ መገኘት ነው። w22.01 23 አን. 14-15
የመታሰቢያው በዓል የመጽሐፍ ቅዱስ ንባብ፦ (ቀን ላይ የተከናወኑ ነገሮች፦ ኒሳን 10) ማቴዎስ 21:18, 19፤ 21:12, 13፤ ዮሐንስ 12:20-50