ቅዳሜ፣ ጥር 24
ለራስህና ለምታስተምረው ትምህርት ምንጊዜም ትኩረት ስጥ።—1 ጢሞ. 4:16
ለይሖዋ እና ለሰዎች ባለን ፍቅር ላይ በማተኮር ለስብከቱ ሥራ ያለንን ቅንዓት ማሳደግ እንችላለን። (ማቴ. 22:37-39) ይሖዋ በዚህ ሥራ ስንካፈል ምን ያህል እንደሚደሰትና ሰዎች መጽሐፍ ቅዱስን ማጥናት ሲጀምሩ የሚሰማቸውን ደስታ በዓይነ ሕሊናህ ለመሣል ሞክር! ለመልእክታችን አዎንታዊ ምላሽ የሚሰጡ ሰዎች ስለሚያገኙት መዳንም አስብ። (ዮሐ. 6:40) ሁኔታህ ከቤት ለመውጣት የማይፈቅድልህ ከሆነስ? እንዲህ ከሆነ፣ ለይሖዋና ለሰዎች ያለህን ፍቅር ለማሳየት ማድረግ በምትችለው ነገር ላይ አተኩር። በኮቪድ-19 ወረርሽኝ ወቅት ሳሙኤል እና ዳኒያ በቤታቸው ለመቆየት ተገደው ነበር። በዚህ አስቸጋሪ ጊዜ አዘውትረው በስልክና በደብዳቤ ምሥክርነት ይካፈሉ እንዲሁም በዙም አማካኝነት የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናቶችን ይመሩ ነበር። ሳሙኤል እና ዳኒያ ሁኔታቸው ቢገድባቸውም የሚችሉትን ነገር ሁሉ አድርገዋል፤ በዚህም ደስታ አግኝተዋል። w24.04 18-19 አን. 15-16
እሁድ፣ ጥር 25
ባለሙያ ሚስትን ማን ሊያገኛት ይችላል? ዋጋዋ ከዛጎል እጅግ ይበልጣል።—ምሳሌ 31:10
ደስተኛ ለመሆን ትዳር መመሥረት የግድ አስፈላጊ ባይሆንም ወጣትም ሆኑ አረጋውያን በርካታ ያላገቡ ክርስቲያኖች ማግባት ይፈልጋሉ። እርግጥ ነው፣ መጠናናት ከመጀመርህ በፊት በኢኮኖሚ፣ በመንፈሳዊና በስሜታዊ ለትዳር ዝግጁ መሆን ይኖርብሃል። (1 ቆሮ. 7:36) መጠናናት ከመጀመርህ በፊት ምን ዓይነት የትዳር ጓደኛ እንደምትፈልግ ቆም ብለህ ማሰብህ ጠቃሚ ነው። እንዲህ ካላደረግክ፣ ጥሩ የትዳር አጋር ልትሆንህ የምትችልን ሴት ችላ ብለህ ልታልፍ ወይም ከማትሆንህ ሴት ጋር መጠናናት ልትጀምር ትችላለህ። እርግጥ ነው፣ ለትዳር የምታስባት ሴት የተጠመቀች ክርስቲያን መሆን አለባት። (1 ቆሮ. 7:39) ያም ቢሆን ሁሉም የተጠመቁ እህቶች ጥሩ የትዳር አጋር ይሆኑሃል ማለት አይደለም። ስለዚህ ራስህን እንዲህ እያልክ ጠይቅ፦ ‘ግቤ ምንድን ነው? ላገባት የማስባት እህት የግድ እንዲኖሯት የምፈልጋቸው ባሕርያት የትኞቹ ናቸው? የምጠብቀው ነገር ምክንያታዊ ነው?’ w24.05 20 አን. 1፤ 21 አን. 3
ሰኞ፣ ጥር 26
አንዳችሁ ለሌላው ደጎች . . . ሁኑ።—ኤፌ. 4:32
በምትጠናኑበት ጊዜ አልፎ አልፎ የሚያጋጥሙ ችግሮችንና አለመግባባቶችን መፍታት የምትችሉት እንዴት ነው? አለመግባባት መፈጠሩ የምትጣጣሙ ሰዎች አይደላችሁም ማለት ነው? ላይሆን ይችላል፤ ሁሉም ጥንዶች አለመግባባት ያጋጥማቸዋል። ጠንካራ ትዳር ልዩነቶቻቸውን ለማሸነፍ ተባብረው መሥራት የሚችሉ ሁለት ሰዎች ጥምረት ነው። ስለዚህ በአሁኑ ወቅት ችግሮቻችሁን የምትፈቱበት መንገድ የሰመረ ትዳር መመሥረት የምትችሉ መሆን አለመሆኑን ሊጠቁም ይችላል። እንዲህ እያላችሁ ራሳችሁን ጠይቁ፦ ‘በእርጋታና በአክብሮት መወያየት እንችላለን? ድክመቶቻችንን አምነን ለመቀበልና ማሻሻያ ለማድረግ ፈቃደኞች ነን? እሺ ለማለት፣ ይቅርታ ለመጠየቅና ይቅር ለማለት ፈጣኖች ነን?’ (ኤፌ. 4:31) ይሁንና በምትጠናኑበት ወቅት ሁልጊዜ የምትጣሉ ወይም የምትጨቃጨቁ ከሆነ ከተጋባችሁ በኋላ ሁኔታው ይሻሻላል ብሎ መጠበቅ ምክንያታዊ አይደለም። ግለሰቡ ለእናንተ እንደማይሆናችሁ ከተገነዘባችሁ ግንኙነታችሁን ማቆሙ ለሁለታችሁም የተሻለ ነው። w24.05 29 አን. 12